Monday 30 June 2014

የታሰሩ የኦሮሞ ተማሪዎች ጉዳይ ትኩረት ሊነፈገው አይገባም

ትናንትና ከዞን ናይኖች መካከል ሶስቱ ፍርድቤት ቀርበው ፖሊስ ሌላ የጊዜ ቀጠሮ የጠየቀባቸው ሲሆን ፍርድ ቤቱ ሁለት ሳምንት ገደማ እንደፈቀደ ሰምተናል። በጸረ ሽብርተኝነት ህጉ እያንዳንዱ የጊዜ ቀጠሮ ከሃያ ስምንት ቀን ማነስ የሌለበት ሆኖ ሳለ( አጠቃላይ የምርመራ ጊዜው ከ አራት ወር እስካልበለጠ ድረስ) አነስ ያለ የጊዜ ቀጠሮ የተሰጠበት ምክንያት ጉዳዩ ተመልሶ በወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት መታየት በመጀመሩ ይሁን ወይም በዳኛው ስ ህተት ወይም ደግሞ ጉዳዩ ከቀሪዎቹ ተከሳሾች ጋር በሁለት ሳምንት በመለያየቱ ያንን ለማስተካከል ከመንግስት በተዘዋዋሪ በመጣ ትእዛዝ ለማወቅ አይቻልም። የሆነው ሆኖ ስለዚህ ጉዳይ ለመጻፍ ሳስብ አንዳንድ የፌስ ቡክ ወዳጆቼ  ከተቃውሞ ሰልፉ ጋር በተያያዘ የታሰሩ የኦሮሞ ተማሪዎች ይፈቱ የሚል ጥሪ እያቀረቡ እንደሆነ ተረዳሁ። ዞን ናይኖች እንዲህ በብዙ ሰው ትኩረት ውስጥ ሆነው ሳለ እስካሁን ባለው ሂደት የታዩና የተሰሙ አንዳንድ ሁኔታዎችን ስናስብ፣ በተመሳሳይ የህዝብና የሚዲያ ትኩረት ውስጥ ያልገቡ በየቦታው ከተቃውሞ ሰልፉ ጋር በተያያዘ የታሰሩ ኢትዮጵያውያን ለመብት ጥሰትና ለእንግልት ከዞን ናይኖችም በላይ የተጋለጡ እንደሆነ ልብ ልንል ይገባል። ከዞን ናይኖች ጉዳይ ጋር እያዛመድን አንዳንድ ጥያቄዎች ማንሳት እንችላለን። 

የታሰሩ የኦርሞ ተማሪዎች በተያዙ በ አርባ ስምንት ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት ቀርበዋል ወይ?
በዞን ናይኖች ክስ ሂደት መንግስት በትክክል ከሰራቸው ነገሮች አንዱ በወንጀል ጠርጥሪያቸዋለሁ ብሎ ከያዛቸው በኋላ በ አርባ ስምንት ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት ማቅረቡ ነበር። ፍርድ ቤት የመቅረባቸው አላማ የሆነው የተያዙበትን ምክንያት በቂነት የማረጋገጥና ከጠበቃና ከዘመድ ተለይተው እንግልት እንዳይደርስባቸው የማድረግ አላማ በሚገባ ተደርጓል ባይባልም፣ ፍርድ ቤት በጊዜው መቅረባቸው ባያስመሰግንም አያስወቅስም። ከተቃውሞ ሰልፉ በኋላ የተያዙ የኦሮሞ ተማሪዎች በእርግጥ የተያዙት በወንጀል ተጠርጥረው ከሆነ  ተመሳሳይ በቶሎ ፍርድ ቤት የማቅረብ ተግባር መፈጸሙን አናውቅም። 

ተማሪዎቹ ከተለያየ አይነት የእንግልት እና የማሰቃየት ተግባር ተጠብቀዋል ወይ? 
የብዙዎቻችንን ትኩረት አግኝቶ የነበረው የዞን ናይኖች ጉዳይ ልጆቹን በ አርባ ስምንት ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት በማቅረብ ቢጀመርም፣ ለቀጣዮቹ አስር ቀናት ከቤተሰብና ከጠበቃ ለይቶ በማቆየት የጊዜው መንግስት እንደዚህ ትኩረትን በሚስቡ እና ሰው ሁሉ በሚከታተላቸው ጉዳዮች እንኳን ለ አገሪቱ ህገ መንግስትና መብትን የሚደነግጉ ህጎች ያለውን ንቀት አሳይቷል። ይህ ሁኔታ ትኩረት ባገኘው የዞን ናይኖች ጉዳይ እንዲህ ያለው ተግባር ከተፈጸመ፣ በተለያዩ የ አገሪቱ ክፍሎች በብዛት ለእስራት በበቁትና ቁጥራቸው ተለይቶ በማይታወቅ ወጣቶች ላይ ምን ተደርጎ ይሆን ብለን እንድንጠይቅ ያደርገናል። ከዞን ናይን ታሳሪዎች መካከል የተወሰኑት ፍርድ ቤት ቀርበው የማሰቃየት ተግባር ተፈጽሞብናል ሲሉ በተናገሩት ላይ ተመስርቶ የተደረገ የምርመራም ሆነ የማጣራት ተግባር አለመኖሩ የጊዜው መንግስት እንዲህ ያለውን አሳፋሪ ተግባር ለመከላከልም ሆነ ሲደርስ እርማት ለመውሰድ ተቃማዊም ሆነ የ አሰራር ዝግጁነቱ እንደሌለው ግልጽ አድርጎታል። እንዲህ ትኩረት በሳበ ጉዳይ ላይ እንዲህ ያለው ግዴለሽነትና ማን አለብኝነት  ከተስተዋለ በኦሮምያ የተለያዩ አካባቢዎች በታሰሩ ተማሪዎች ላይ ይህን የመሳሰለው ነገር እንዳልተፈጸመ ምን ማረጋገጫ ይኖራል? አያያዛቸው ከዞን ናይኖች አያያዝ የባሰ እንደሚሆን ግን መገመት ይቻላል። በፖሊስ ይዞታ ውስጥ ሆኖ የሞተ ተማሪ እንዳለ ሁሉ ሰምተናል። ይህን ተከትሎ ምን ምርመራ ተደረገ? ምናልባትም ምንም። እንደ ሰብ አዊ መብት ኮሚሽን ያሉ ተቋማት ከውጭ የሰብ አዊ መብት ተሟጋቾች ጋር በመሟገት የ አገሪቱን ገጽታ ላለማበላሸት እየጣሩ እንደሆነ ነግረውናል። የቱሪዚም ቢሮ ናቸው እንዴ እነሱ?

አንዳንድ ሰዎች ተጠርጣሪዎች በቀጥታ ፍርድ ቤት እየቀረቡ የማሰቃየት ተግባር ተፈጽሞብናል፣ እንዲህ እና እንዲያ ያለው እንግልት ተደርጎብናል እያሉ እንኳን አንዳች ድንጋጤና ጭንቀት አይሰማቸውም። ለምን እንደሆነ አይገባኝም። በደርግ ጊዜ ያ ሁሉ የማሰቃየት ተግባር በኢትዮጵያ ወጣቶች ላይ ሲፈጸም የወቅቱ ስርዓት በንጉሱ ጊዜ የወጡ ተጠርጣሪዎች በተያዙ በአርባ ስምንት ሰዓት ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ፣ ተገደው ቃላቸውን እንዳይሰጡ፣ ጠበቃ እንዲያገኛቸው ወዘተ የሚደነግጉ ህጎችን እንደማይጠቅም የፍ ትህ አተያይ ቆጥሮ ችላ ብሏቸው  እንደነበረ ልንረሳው አይገባም። አሁንም በህገ መንግስቱ እና በሌሎች ህጎች ላይ የተቀመጡ የዜጎችን መብቶች በተመለከተ ከርዕዮተ አለማዊ ዝንባሌ የሚመነጭ የንቀት አተያይ በ አንዳንድ ሰዎች ዘንድ አስተውላለሁ። ስለ መብት የሚያወራ ሰው ስለ አገሪቱ መልካም ነገር ማውራት የማይፈልግ እንደሆነ አድርገው የሚቆጥሩም አሉ። ይሄ ትክክል አይደለም። ስ ለ አገሩቱ መልካም መልካሙን ብቻ መርጦ ማውራት አገርን መውደድ አይደለም። ደርግም በጣም ለብዙ ዘመናት በሰሜን የነበረውን ጦርነት ከኢትዮጵያ ህዝብ አይንና ጆሮ ደብቆ እንደኖረ ልናስታውስ ይገባል። ርሃብንም የደበቅንበትና ሰው በጠኔ እንዲሞት የፈቀድንበት ታሪክ አለን። በቀይ ሽብርና ከዚያም በኋላ በ አገሪቱ ውስጥ የሆነውንና የተደረገውን ኢሰብዓዊ ድርጊት በሚገባ አውግዘን እንዳይደገም ለራሳችን ቃል ገብተን እየኖርን አይደለም ያለነው። ይሄ ደግሞ መሻሻሎች ቢኖሩም ከግፍ ቀለበት እንዳንወጣ አድርጎናል። የለመለመ መስክና የተንጣለለ አስፋልት እያሳዩ መመጻደቅ አገርን መውደድ አይደለም። የ አሜሪካ ጦር በኢራቅ አቡግራይብ እስር ቤት የፈጸመውን ግፍ ያጋለጡት እና ያራገቡት እንደ አምንስቲ ኢንተርናሽና ያሉ የሰብ አዊ መብት ተሟጋቾች ናቸው። ተመሳሳይ ድርጅት የተቃውሞ ሰልፎቹን ተከትሎ እንዳወጣው ያለውን አይነት መግለጫ በትኩረት አይተን እርምጃ ብንወስድ የምንጠቅመው እኛ ነን። የምናሰቃየው፣ የምናዋክበው እና የምናንገላታው እንደ አሜሪካኖቹ እንኳን በሰው አገር ሄደን አይደለም። የገዛ ህዝባችንን ነው። ያንቀላፋ ህሊናችን ሊነቃ ይገባል።  በየ እስር ቤቱ ያሉ የኦሮሞ ተማሪዎች ላይ የሚፈጸመባቸውን ማሰቃየት፣ በደልና እንግልት ሊቆም ይገባል። ነጻነታቸውንም ማግኘት አለባቸው። 


Wednesday 21 May 2014

ህግና ፍትህ- በቅርቡ በኦሮምያ የተከሰተው የተቃውሞ ሰልፍ ሂደት በገለልተኛ አካል መመርመር አለበት



ብዙ ሰዎች ህግን ያከብራሉ፤ መንግስታትም ሰዎች ለህግ እና ለህግ ስርዓት በሚሰጡት ክብር ይጠቀማሉ። ህግ ግን የተገቢነት ብቸኛ መለኪያ አይደለም። ምክንያቱም ህግ ጉልበተኞች ደካሞችን የሚጨፈልቁበት የጭቆና መሳሪያ ሆኖ ሊያገለግል ይችላልና ነው። ከጥንትም ጀምሮ ብዙ ሰዎች ፍትህ ማለት የተጻፈው ህግ እንዳለ መተግበር ነው ብለው ያስባሉ። ህጉ ቁራሽ ዳቦ እርቦት የሰረቀ ሰው መገደል አለበት ካለ፣ ሰውዬው ይህን ማድረጉ እስከተረጋገጠ ድረስ መገደሉ ፍትሃዊ ነው ይላሉ። ህጉ ንጉሱን የሰደበ መገረፍ አለበት ካለ፣ አጥፊው ንጉሱን መስደቡ እስከተረጋገጠ ድረስ መገረፍ አለበት ይላሉ። ህጉ ሃይማኖት የቀየረ ሰው ተሰቅሎ መገደል አለበት ካለ፣ ይሄንኑ ነገር ማድረግ ፍትሃዊ ነው ይላሉ።

ህግ ራሱ መልሶ የተገቢነት ጥያቄ ይቀርብበታል። ፍትህ ወረቀት ላይ የተጻፈውን ህግ ከመተግበር የዘለለና፣ ህግ ራሱ ተገቢነቱ የሚለካበት ሚዛን ተደርጎ የሚታይበትም ሁኔታ አለ። በተለይ የመንግስት ስልጣን በተቀየረ ጊዜ፣ ወይም አንድ ሃይለኛ ጉልበት የነበረው መንግስት በጦርነት በተሸነፈ ጊዜ ሁሉ በስልጣን ላይ በነበረበት ጊዜ ህጋዊ ተብለው የተፈጸሙ ነገሮች ሁሉ እንደገና በወንጀልነት ይጠየቃሉ። ከሁለተኛው አለም ጦርነት መገባደድ በፊት በናዚ ጀርመን እና በጃፓንም ሃይሎች የተፈጸሙ ወንጀሎች ለፍርድ ቀርበዋል። ከዚያም በኋላ በየጊዜው በተለያዩ አገራት የነበሩ አምባገነኖች የፈጸሟቸው ወንጀሎች ከስልጣን ከወረዱ በኋላ ለፍርድ ዳኝነት ቀርበዋል። አሁን ህግን ሁሉ እንዳለ መተግበር እንደ ፍትህ የሚቆጠርበት ጊዜ አክትሟል። ከተባበሩት መንግስታት መቋቋም በኋላ የሰብዓዊ መብት ጽንሰ ሃሳብ ማነኛውንም ህጋዊ ተብሎ የሚፈጸም ተግባር ተገቢነት ለመመዘን የሚያስችል የፍትህ ሚዛን ሆኗል። ዛሬ በአገረ ሱዳን ህግ መሰረት በፍርድ ቤት ሞት የተፈረደባት እርጉዝ ሴት እንዳትገደል አለም የሚጮኸው በዚህ የፍትህ ሚዛን ተለክቶ ህጋዊ የተባለው ነገር ቀሎ ስለሚታይ ነው።

ኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶችን በመቀበል ከአገራት ባትዘገይም፣ ብዙ ጊዜ መብቶቹን ለማክበር የሚያስፈልገው ቁርጠኝነት፣ ተቋማት፣ አስራር እና ባህል እጥረት አንቆ ይይዛታል። ንጉሱ በምዕራባውያን አርቃቂዎች ያሰሯቸው ህጎች የህዝብረተሰቡን ባህልና አኗኗር የሚያንጸባርቁ ባይሆኑም፣ ዜጎችን በተሻለ ክብር ለማስተናገድ የህዝቡንም ባህል በህጎቹ አቅጣጫ ለማስኬድ ጥሩ መነሻ ነበሩ። ደርግ በርዕዮተ አለማዊ ምክንያቶች እነዚያን ህጎች ችላ አላቸው።በወቅቱ ነገሮች ከሚታዩበት ርዕዮተ አለማዊ መነጸር በመነሳት፣ ህጉን ላወጣው ስርዓተ ማህበረሰብ በነበረው ንቀት የተነሳ በህጉ ውስጥ የተካተቱት ጠቃሚ ነጥቦች ተረሱ። አሁን ህገ መንግስታዊ እውቅና ያላቸው ነጻ ሆኖ የመገመት መብት፣ በራስ ላይ እንዲመሰክሩ ያለመገደድ መብት፣ ጠበቃ በተቻለ ፍጥነት የማግኘት መብት ወዘተ በሙሉ በንጉሱ ጊዜ በወጡ ህጎች ውስጥ የተካተቱ ነበሩ። እነዛ ሁሉ ችላ ተብለው ሰዎች ያለ ፍርድ ተገደሉ። ህግን የጨቋኞች መሳሪያ ብለው የሚጠየፉት፣ ያለ ህግ ድጋፍ አብዮታዊ እርምጃን መውሰድ ፍትህ ነው ብለው ወሰዱት።   በደርግ ጊዜ በዋና ዋና የ አገሪቱ ከተሞች የተፈጸሙ ግድያዎች፣ ማሰቃየቶች ሁሉ በተፈጸሙበት ወቅት አብዮታዊ እርምጃዎች ተብለው ቢንቆለጳጰሱም፣ ተጎጅዎቹም ጸረ ህዝቦች ተብለው ስርዓት ያለው ቀብር ቢነፈጉም፣ ጊዜው ሲደርስ እንባቸውን እንዲውጡ የተጠየቁት ሰዎች ዝም ባሰኟቸው አሳሪዎቻቸው ፊት ለመመስከር በቅተዋል።

አሁንም ለህግ ከሚሰጠው ክብር የመንግስትን ቅቡልነት ብቻ ለማግኘት እየተጠቀሙ፣ በእርግጥ ግን ህግን በከፍተኛ ንቀት ማየት አልቆመም። የጊዜው መንግስት ሰዎች ከደርግ ጋር ከተመሳሳይ የርዕዮተ አለም ወንዝ ስለሚቀዱ፣ አሁንም የህገ መንግስቱ የሰብዓዊ መብት አንቀጾች በንቀት ይታያሉ። በተለይ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች የሚባሉት የኢኮኖሚ፣ ማህበራዊ እና የባህል መብቶች ከሚባሉት እንዲሁም ከቡድን መብቶች ባነሰ አይን የሚታዩ ይመስላል።

በጊዜው መንግስት የስልጣን ቆይታ በፊት ከነበረው የተሻሻለ ብዙ ነገር እንዳለ ባይካድም፣ አሁንም ቢሆን አገሪቱ አለኝ በምትለው ህገ መንግስትና፣ አጽድቂያቸዋለሁ የህጎቼም አካል ናቸው በምትላቸው አለም አቀፍ ህጎች መሰረት የመንግስትን ስልጣን የመገደብ ጉድለት አለ። ይሄ ጉድለት ከመቼውም ጊዜ በላይ የተወሰነ የህብረተሰብ ክፍል በተለያዩ ምክንያቶች መብቴ የሚለውን ለመጠየቅ ሲሞክር፣ አንዳንዴም ሃይል የቀላቀሉ ሰላማዊ ሰልፎች ሲደረጉ ጎልቶ ይወጣል። በቅርቡ በኦሮምያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች የተከሰተውን ሰላማዊ ሰልፍ ተከትሎ የሆነውም ይሄው ነው። በአለም አቀፍ ሰብዓዊ መብት ህግ መሰረት በአጠቃላይ ሰላማዊ ሰልፎች፣ ሃይል የቀላቀሉም ቢሆኑ እንዴት መስተናገድ እንዳለባቸው የሚዘረዝር አሰራር አለ። በቅርቡ የተካሄዱትን ሰልፎች እና የደረሰውን ጉዳት ተከትሎ አምንስቲ ኢንተርናሽናል ያወጣው መግለጫ ምን ምን መደረግ እንዳለበት በግልጽ ይዘረዝራል። አገር ውስጥም ቢሆን ውስጥ በነዚህ ሁኔታዎች ምን መደረግ እንዳለበት ጠንቅቀው የሚያውቁ ብዙ ባለሙያዎች አሉ።

ባሁኑ ሰዓት ከሁሉም በላይ የሚያስፈልገው ጉዳዩን የሚመረምር እና በተቃውሞ ሰልፍ ሂደቱ የነበረውን የመንግስት የሃይል አጠቃቀም፣ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የታሰሩ ዜጎች ቁጥር፣ ከታሰሩ በኋላ የድብደባ እና የማሰቃየት ተግባራት መፈጸም አለመፈጸሙን ወዘተ በገለልተኝነት መርምሮ ለመንግስትና ለህዝብ የሚያቀርብ ገለልተኛ አካል ነው።የመንግስት ሃይሎች ሃይል ተጠቅመው ህይወት ከጠፋ፣ ነገሩ ስለተፈጸመበት ሁኔታ መልሶ ምርመራ ማድረግና የሃይል አጠቃቀሙ ላይ ችግር ከነበረ ጥፋተኞችን መቅጣት በህይወት የመኖር መብትን የማክበር ግዴታ አካል ተደርጎ የሚታይ አሰራር ነው። የጠፋ ህይወት አይመለስም። ነገርግን ጉዳዩን መርምሮ፣ ስ ህተቶችን ማረም ለወደፊቱ ከሚሰጠው ጥቅም አንጻር አንድ ሃላፊነት ከሚሰማው ስርዓት የሚጠበቅ ነው። ዝም ብሎ በጭፍን ሁሉንም የፖሊስ አሰራር ልክ ነው ማለት፣ ወይም ሰልፈኞቹን ተጠያቂ ማድረግ ጸረ ሰብዓዊ መብት የሆነ አሰራር ነው።  

 በመሰረቱ ሃይል የቀላቀለ ሰልፍ የማይደረግበት አገር የለም። ከሰብዓዊ መብት አንጻር ጥቅም ላይ መዋል ያለበት መርህ ግን ተመሳሳይ ነው። ከተወሰኑ አመታት በፊት በእንግሊዝ የአንድ ወጣትን በፖሊስ መገደል ተከትሎ የተነሳውን ሁከት ማስታወስ ይቻላል። በተለያዩ ከተማዎች በነበረው ሁከት የሞቱት ሰዎች ቁጥር ባልሳሳት ከአምስት አይበልጥም። በሂደቱ የታሰሩት ሰዎችም ቁጥር ግልጽ ሆኖ የሚታወቅ ነበር። ኢትዮጵያ ውስጥ የህግ ማዕቀፉ ቢኖርም እንደዚህ አይነት አሰራሮችን በማስፈን ፋንታ መንግስት በመሰረቱ እስካሁንም የሚሰራው ባረጀ እና ባፈጀ አካሄድ ነው። መርሁም አንድ ይመስላል፤ ፕሮፓጋንዳ ፕሮፓጋንዳ አሁንም ፕሮፓጋንዳ። ከዚህ በፊትም ከቶርቸር ጋር አያይዤ በጻፍኩት ጽሁፍ ላይ እንደጠቀስኩት፣ እንደዚህ የሚቀጥል ከሆነ ይህም ስርዓት እንደ ደርግ እያሉ ግን ችላ በተባሉ በራሱ ህጎች የሚጠየቅበት ቀን ይመጣል። መንግስት ህገ መንግስታዊ ስርዓቱ ሲል፣ ያለው ህገ መንግስት በስልጣን ላይ ያለውን ስርዓት ከተቃውሞ ለመከላከል የወጣ ይመስል፣ የዜጎችን መብት የሚዘረዝረው ክፍል ይረሳል። ይህን የብዙ ሰዎች ህይወት የተቀጠፈበትን የተቃውሞ ሰልፍ ሂደት በገለልተኛ አካል አስመርምሮ ጥፋተኞች ሃላፊነት እንዲወስዱ፣ ተጎጅዎች ካሳ እንዲያገኙ፣ ህዝብም እውነቱን እንዲያውቅ ካላደረገ የሟቾቹን በህይወት የመኖር ሰብዓዊ መብት እንደጣሰ እንደሚቆጠር ሊታወቅ ይገባል።  ሁሉንም የሚጠቅመው አካሄድ ግን ቀላል ነው። ሰብዓዊ መብትን ለማክበር የሚጥርና ስህተት ሲሰራ የሚያርም አሰራር መፍጠር የማይቻል አይደለም። ይሄ ደግሞ አሁን በሂደት ካልተፈጠረ ጉልቻም ቢቀየር እንኳን የወጡ ጣዕም አይቀየረም። መቼም ህዝብ ከሌላ አገር ማስመጣት አይቻልም።



Sunday 18 May 2014

የቴድሮስ አድሃኖምን የፌስ ቡክ ፔጅ አንላይክ ከማድረጌ በፊት የጻፍኩት መግቢያ



ዞን ናይኖች ይፈቱ እያልን ስንጮህ ጭሆታችንን እንደ ሙዚቃ እያጣጣሙት መሆኑን ለማስረዳት ያህል እንዲያውም የጠረጠርናቸው በሽብርተኝነት ነው ብለውን አረፉ። እንግዲህ ኢሜላቸው ሲበረበር ህገመንግስታዊ ያልሆነ ሃሳብ ተገኞቶበት ይሆናል። መቼስ ምን ይደረግ? እነሱ በድርጊት የማይጥሱት፣ ግለሰቦች ወይም ተቃዋሚዎቻቸው በሃሳብ የሚጥሱት ህገ መንግስት ነው ያለው።  ከዞን ናይኖች መታሰር ወዲህ ስለ አንድ ነገር ልጽፍ እነሳና አቋርጬ እተወዋለሁ። "ምን ዋጋ አለው?" እልና እተወዋለሁ። አንዳንድ አገራችንን በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ የፌስ ቡክ ውይይት ሳይ ሁሉ እጅ እጅ ይለኛል። እነሱም የፈለጉት ይህንን ነው። ያሰሩት ዞን ናይኖችን ይሁን እንጅ ለማሸማቀቅ የፈለጉት ሁላችንንም ነው። መልእክቱ ለእያንዳንዱ በኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባኛል ብሎ በድፍረት ቀና ብሎ መናገር የሚጀምርንና የሚያስብን ሰው ሁሉ የሚመለከት ነው። ብርቱካን ሚዴቅሳ ላይ የሆነውም ይሄ ነው። አገር ውስጥ ሆኖ መንግስትን መቃወም፣ በራስ ስም እና ምስል በግልጽ ተቃውሞ መናገር መንግስትን ማመንንም ይጠይቃል። እንጅ እንደ ኤርትራ ባለ አገር ለምሳሌ ዞን ናይኖችን የመሰለ ሰው ማግኘት አይቻልም። ይሄ መንግስት ዞን ናይኖች ላይ እርምጃ በመውሰድ የፍርሃቱን መጠን ብቻ ሳይሆን ያሳየው፣ ዞን ናይኖች በቀጥታም ባይሆን በስር አቱ ላይ ያሳደሩትን እምነት ነው የሰበረው። በግልጽ  የ አይነ መረብ ዘመቻ ሲያካሂዱ የነበሩ ሰዎችን በህብዕ እንደተደራጁ አድርጎ ማቅረብ፣ ተልካሻ መከራከሪያዎችን እያቀረቡ ትልቅ ነገር እንደተነገረ እያስመሰሉ መመጻደቅ፣ ያንንም በህግ የበላይነት ስም እንደሚደረግ እያስመሰሉ ራስን ማድነቅ ከመደጋገሙ የተነሳ እንኳን በታሰሩት ላይ ባልታሰርነው በ አንዳንዶቻችን ላይም የስነ ልቦና ቶርቸር እየተፈጸመብን እንዳለ እንድቆጥረው ያደርገኛል።

 ስለዚህ ጉዳይ ስንወያይ አንድ ጓደኛዬ በቀልድ መልክ "ቀጣይማ የምትታሰረው አንተ ነህ" ይለኛል። እኔ ደግሞ መልሼ በቀልድ መልክ "አንተን ካሰሩህ መሳሪያ ይዤ ወደ ጫካ ነው የምሄደው" እለዋለሁ። ከዛ ሁለታችንም እንሳሳቃለን። ቀጠል አደርግና "እኔም ብታሰር  ፌስ ቡክ ላይ ካሉ ሰዎች ውስጥ እነ እንትናና እነ እንትና "መንግስት ያደረገው ልክ ነው" ወይም ደግሞ "ፍትሃዊው የህግ ስርአታችን የሚለውን እስክንሰማ ድረስ እስራቱን አንቃወምም ይሉ ይሆናል እኮ" እለዋለሁ። እውነት ነው። ናትናኤል  በቅርቡ ምናልባትም ተመሳሳይ ውይይት ከቤተሰቦቹ እና ከቅርብ ጓደኞቹ ጋር እንዳደረገ መገመት እችላለሁ። እኔን ከናትናኤል የሚለየኝ ነገር ቢኖር እኔ የሱን ያህል ቆራጥነት የሌለኝ መሆኔ ይመስለኛል። እሱ ዲሞክራሲን ለኢትዮጵያ በሚመኘው ልክ እኔ አልመኝም ይሆናል። አሁን ከታሰሩት ውስጥ ከበፍቃዱ ውጭ የፌስ ቡክ ጓደኛዬ የሆነው እሱ ነው። በጣም አጨቃጫቂ በሆኑ ወቅቶች እንኳን ሰውን የሚያስቀይም ነገር ሲናገር አይቼው አላውቅም። አስታውሳለሁ መለስ መሞቱ እንደተረጋገጠ  "የኢትዮጵያ ህዝብ መለስን አልቅሶ ይቀብረዋል፤ ሃዘኑም የማስመሰል አይሆንም፤ ለዚህም በጣም እርግጠኛ ነኝ፤ ሌላ ነገር የሚጠብቅ ካለ የስነ ልቦና ዝግጅት ያድርግ" አልኩ። በዚህ አባባሌ ውስጥ የሚሆነውን ከመተንበይ አልፌ እንዲሆን የምፈልገውን እየተናገርኩ በመሆኑ በእርጋታ በአስተያየቴ እንደማይስማማ ሲገልጽልኝ አስታውሳለሁ። ከዚያ ውጭ ሌላው ቀርቶ የኢትዮጵያ የሰ ብ ዓዊ መብት አያያዝ በኃይለ ማርያም አስተዳደር ሊሻሻል ይችላል የሚለውን የቀን ቅዠቴን ፌስ ቡክ ላይ አክቲቭ በነበረበት ጊዜ ይጋራኝ እንደነበር አስታውሳለሁ። ይሄ አስተዳደር በሽብርተኝነት ተጠርጥሮ የሚታሰርበት ይሆናል ብሎ ግን ጨርሶ የገመተ አይመስለኝም። 


የነዚህ ልጆች መታሰር ቢያንስ  በአይነ መረብ በመሰረትነው የውይይትና የክርክር ማህበረሰብ ላይ የነበረንን የይስሙላ እኩልነት ነው ያፈረሰው። እንደዚህ ቀደሙ እንኳን ለምሳሌ እንደ እስክንድር መንግስትን የሚያበሳጩ ተከታታይ ጽሁፎች አልጻፉም። ከሰብአዊ መብት ተቋማት ጋር መስራት ነውር ነው ከተባለ ያንን እንዲያቋርጡ ጠርቶ ማናገር በቂ ነበር። በግሌ እንደምጠረጥረው አርቲክል አስራ ዘጠኝ የተባለው ድርጅት ገና በመስከረም ወር ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብ አዊ መብት ጉባኤ በ አመቱ ኢትዮጵያ ላይ ለሚያካሂደው ግምገማ እንዲረዳ በሚል ያወጣው በጣም ዝርዝር ሪፖርት ውስጥ ምናልባት እነዚህ ልጆች ተሳትፈው ይሆናል።ለሰ ብ አዊ መብት መከበር መስራት ወንጀል ከሆነ፣ የሚፈለገው ሰብአዊ መብትን መጣስ ህጋዊ እንዲሆን ነው ማለት ነው። በጥር ወር ይሄው ድርጅት ሰርቶ ባወጣው በኢትዮጵያ ስላለው ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ሁኔታ በሚዳስስ ዶክመንታሪ ላይ አሁን ከታሰሩት የዞን ናይን አባላት መካከል ሁለቱ ቃለ ምልልስ ተደርጎላቸዋል። አርቲክል አስራ ዘጠኝ የተባለው ድርጅት እነዚህን ልጆች ማግኘቱን ለመደበቅ ያደረገው አንዳችም ሙከራ እንዳልነበረ ያሳያል። ሌላው ቀርቶ የተለየ እቅድ እንደነበረ ለማስመሰል እየተደረገ የሚቀርበው ድርጅቱ ለጋዜጠኞች የሚሰጠው ሴኩሪቲ ነክ ስልጠና በዚሁ ዶክመንታሪ ላይ በድርጅቱ የአፍሪካ ሃላፊ በግልጽ ይጠቀሳል። እናም በጋሃድና በግልጽ የሆነውን ነገር ልክ በህቡ እንደተካሄደ ወንጀል እያደረጉ ሰዎችን ማዋከብ፣ ነጻነታቸውን መንፈግ፣ የግል ህይወታቸውን እና ከሰዎች ጋር የሚያደርጉትን የሃሳብ ልውውጥ እየበረበሩ ወንጀል የሚሆን ነገር በእግር በፈረስ መፈለግ የፍትህ ስራ ሳይሆን በራሱ ወንጀል ነው። አዎ መንግስት ይፈራል፤ የህዝብ አመጽ ይፈራል። በተለያየ ምክንያት ሰዎች ይህን አይነት አመጽ ሊናፍቁ፣ ሊፈልጉ፣ እንደሚፈልጉ ሊናገሩ ይችላሉ። መንግስት ስለሚፈራ ብቻ ግን ሳይተነኮስ፣ ይሄ ነው የሚባል ነገር ሳይፈጠር እየዘለለ ሰላማዊ ዜጎችን እያነቀ ወደ እስር ቤት የሚወስድ ከሆነ ፍርሃቱ ወደ በሽታ ተቀየረ ማለት ነው። ፍርሃት ሲበዛ ደግሞ ጥሩ አይደለም። ባገራችን "የፈሩት ይደርሳል፣ የጠሉት ይወርሳል" የሚባል አባባል አለ። 


 የኢትዮጵያ ህዝብ ስርአቱን በ አመጽ መቀየር ቢፈልግ ኖሮ መለስ ታመመ ተብሎ ምድረ ኢህአዴግ ሲሸበር አያለቀሰም እየጸለየም ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር እንዲኖር በመፍቀድ ፋንታ አጋጣሚዉን ተጠቅሞ የሚፈራውን ነገር ባደረገ ነበር። በነገራችን ላይ በወቅቱ እየቀጠለ የነበረው የሙስሊሞች ተቃውሞ እንኳን በሃዘኑ ምክንያት ተቋርጦ እንደነበር ማስታወስ ግድ ይላል።ለ አመጽ የሚያነሳሳ ጥሪ በወቅቱ መኖሩን የሚክድ ሰው የሚኖር አይመስለኝም። ሌሎች ሁኔታዎች እስካልተሟሉ ድረስ ጥሪ ስለተደረገ ብቻ ሰው ለአመጽ አይነሳም።  በሃይለማርያም አስተዳደር በመለስ ጊዜ ከነበረው የሰ ብ አዊ መብት አያያዝ እና የዲሞክራሲ ሁኔታ የሚሻሻል ነገር ይኖራል ብለን ስንጠብቅ የሚሰጠን ምላሽ እነ ናትናኤልን በሽብርተንነት መክሰስ ከሆነ ለያውም በተልካሻ ምክንያት እኔ እንደ ጠብ ያለሽ በዳቦ ነው የምቆጥረው። ይህን የምለው የኢትዮጵያ ህዝብ ዞን ናይኖች ታሰሩ ብሎ ጎዳና ላይ ወጥቶ ፍቱልን ይላል ብዬ አይደለም። የኢትዮጵያ ህዝብ የሚሰጠው የዲሞክራሲ ተስፋ እውነት እየመሰለው ትንሽ ቀና ቀና ከማለት ውጭ የደርግን እና የኢሳያስን ያህል ጭቆና መሸከም የሚችል ህዝብ ነው። 


የጊዜው መንግስት እየሄደበት ያለው አቅጣጫ ሳይተነኮሱ አንድ ሰው ዝም ብሎ ቁጭ ባለበት ሄዶ እንደመደብደብ አይነት ነገር ነው። ዞን ናይኖችን ማሰር ለኔ ያ አይነት እርምጃ ነው። ባጭሩ በግፍ እየተገፋን ነው። ለወትሮው የጊዜው መንግስት ልክ ነው ብዬ በማንምንበት ነጥብ ላይ ተቃዋሚ ነኝ ከሚል ከማንም ጋር ዞሬ የመከራከር ድፍረት ነበረኝ። ይሄ ድፍረት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሸረሸረ መጥቶ ዞን ናይኖቹ ከመታሰራቸው በፊትም ተቃዋሚ ነኝ የሚለውን ወገን ሁሉ ባደባባይ መተቸትን እስከማቆም ድረስ  ደርሻለሁ። እና አንዳንድ ሰዎች ግልጽ አላማና ግብ በሌለው ጭፍን የተቃውሞ ባቡር ውስጥ የተሳፈርኩ እስኪመስላቸው ድረስ በሚያስችል ደረጃ ከነበረኝ አቋም እየተገፋሁ ነው። ባንድ ወቅት አንድ ወዳጄ ለግንቦት ሃያ አከባበር በተዘጋጀ ፕሮግራም ላይ ጥሪ ተልኮለት "ምን እኮ ይሄ ጥሪ ወረቀት ላንተ ነበር መላክ የነበረበት" ብሎ እስኪቀልድብኝ የጊዜውን መንግስት መልካም ጥረቶች በግልጽ ከመናገር ወደ ኋላ የማልል ሰው ነበርኩ። ከዚያ ተነስቼ ነው አሁን ያለሁበት ደረጃ የደረስኩት። በዲሞክራሲ ስርዓት ውስጥ ገዢው ፓርቲ ቢያናድድህ በሆነ መንገድ ትቀጣዋለህ። እንደ ኢትዮጵያ ባለ አገር መንግስት አክት የሚያደርገው ሰዎች ከሌላ ፕላኔት መጥተው ድምጽ የሚሰጡት አስመስሎ ነው። የቅቡልነቱ(legitimacy) ምንጭ የምርጫ ኮሮጆ እንዳልሆነ ስለሚያውቀው ሊሆን ይችላል። ወይም ለአቅመ መናገር የበቁ ዜጎች እንደ መራጭ ዜጋ ሳይሆን እንደ ተፎካካሪ ፓርቲ ስለሚያያቸው ይሆን ይሆናል። ምንም ቢሆን ግን ዞን ናይኖች ላይ እየተሰራው ያለ ግፍ በግሌ በዝምታ አላልፈውም። የምችለው መጻፍ ነው። መጻፌና መናገሬን አላቋርጥም። ይህን የማደርገው ዞን ናይኖች ጓደኞቼ ስለሆኑ አይደለም። በመሰረቱ አሁን ከታሰሩት ውስጥ በአይነ ስጋ አይቼው እንኳን የማውቀው ዘላለምን ብቻ ነው፤ እሱንም በርቀት። ወይም ደግሞ ይህን የማደርገው ህጋዊና ህጋዊ ያልሆነው ነገር በተደበላለቀበት የኢትዮጵያ የተጨማለቀ የፖለቲካ ከባቢ አላማና ግቡ በማይታወቅ የተቃውሞ ፖለቲካ የምሳፈርበት ባቡር ስለሚኖር፣ ወይም የመታሰራቸው ፖለቲካዊ አንድምታ፣ መታሰራቸው በታሳሪዎቹ የግል እና የፖለቲካ ህይወት ያለው ውጤት ወይም ነገሩን ከተቃውሞ ስትራቴጂ እና ከሌሎችም ነጥቦች አንጻር በማየት አይደለም። በቃ በዞን ናይኖች ውስጥ እኔ አለሁ።  የጊዜው መንግስት ላለፉት ሃያ ምናምን ቀናት እያሰማን የነበረውን ጭሆት እንደ ሙዚቃ በመቁጠሩ ይግረማችሁ ብሎ ክሱን ወደ ሽብርተኝነት ለማሳደግ በመወሰኑ ብስጭቴን ለመግለጽ ያህል ላይክ አድርጌ ስከታተለው የነበረውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን የዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ፌስ ቡክ ፔጅ አንላይክ በማድረግ እጀምራለሁ። እርምጃዬ ሊያስቅ ይችላል። ይህን በማድረግ የማስተላልፈው መልዕክት የሚከተለው ነው፤ መንግስትዎ ናትናኤልን አንገቱን ካስድፋ በኋላ፣ የርስዎን ፈገግታ የማይበት አቅም የለኝም። ዞን ናይኖች ሲፈቱ መልሼ እከታተልዎታለሁ። 
ቸር ያሰማን። 

Saturday 10 May 2014

ቶርቸር ይርጋ የሌለው ወንጀል ነው(ክፍል ሁለት)

ቀደም ባለው ጽሁፍ ስለ ጭቃኔ ስለተሞላበት ማሰቃየት የተወሰኑ ሃሳቦችን ወርውሪያለሁ። በወንጀል ተጠርጥረዋል ተብለው በእስር ቤት ከሚገኙት የዞን ናይን አባላት መካከል ፍርድ ቤት ቀርበው ፖሊስ የውስጥ እግራቸውን በመደብደብ የማሰቃየት ተግባር እንደፈጸመባቸው ተናግረዋል የሚለውን አሰቃቂ ዜና ከሰማሁ በኋላ ነበር አስተያየቱን የሰጠሁት። የልጆቹን ያንን ማለት ተከትሎ ፖሊስ ድርጊቱን አልፈጸምንም በሚል ስሜት ማስረጃ የላቸውም አለ መባሉንና ቶርቸር ህገ መንግስታዊ አለመሆኑን መግለጹንም ሰምተናል። የኢትዮጵያ ፖሊስ እንዲህ አያደርግም አይባል ነገር በታሪካችን እና በተሞክሮአችን አስቀያሚ ነገሮችን ያለፍን ህዝቦች ነን። እንደዚህ አይነት ነገር በራሳችንና በምንወዳቸው ሰዎች ላይ ሲፈጸም እንደማንፈልገው ሁሉ በሌሎችም ሰዎች ላይ እንዳይፈጸም ከልባችን የምንፈልግ ከሆነ እንደዚህ አይነት አቤቱታዎችን ቶርቸር ህገ መንግስታዊ አይደለም ከሚል የ አፍ ቸርነት ባለፈ እርምጃዎች መውሰድ አለብን።

እርምጃ መውሰድ ሲባል ምን ማለት ነው የሚለው ላይ ነው በዚህ ጽሁፍ የተወሰነ ነገር ለማለት የምሞክረው። በመጀመሪያ ቶርቸር እጅግ ሰልጥነናል እያሉ በሚመጻደቁ ህዝቦች እየተፈጸመ አንዳንዴ ሲጋለጥ እጅግ አሳፋሪ ቅሌት እየሆነ ያስቸገረ በተለይም ከመስከረም አስራ አንድ ጥቃት በኋላ እና ከኢራቅ አቡግራይብ እስር ቤት የ አሜሪካና የ አጋሮቿ ሃይል የፈጸመውን የሰ ብ አዊ መብት ጥሰት አምንስቲ ኢንተርናሽናል ካጋለጠ በኋላ በእጅጉ አነጋጋሪ የሆነ ጉዳይ ነው። አሁን እኛ የምናወራው ሳሙኤል ጃክሰን በተወነበት Unthinkable በተሰኘ ልብወለድ ፊልም እንደታየው ሶስት ትላልቅ ከተሞችን የሚያወድም ቦንብ ቀብሮ ቃል አልተነፍስም ስለሚል አይነት አሸባሪ አይደለም። እንደዛ ባለው ሁኔታ ስለምንወስደው አቋም በመከራከር ላይሆን የሚችለውን ወይም ከስንት አንዴ የሚሆነውን ሁሌ እንደሚሆን በማስመሰል ትኩረታችንን ከሚሻው ጉዳይ ቀልባችንን ማራቅ አይገባም። ከዚያ ይልቅ ከጎናችን እየተወሰዱ “በህግ ጥላ ስር” ከሆኑ በኋላ እንዲህ አይነት ነገር ተፈጸመብን ሲሉ ምን አይነት ምላሽ ሊኖር ይገባል? እንዲህ አይነት ነገር እንዳይከሰትስ ምን አይነት ጥንቃቄ መወሰድ አለበት? ስለሚለው ነው መጨነቅ ያለብን።

መጀመሪያ የዞን ናይኖችን ጉዳይ እንደ መነሻ እናድርገው እንጅ ይሄ ጉዳይ ከሙስሊም መፍት ሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት መታሰር እና በሽብርተኝነት ከተፈረጁ አካላት ጋር ግንኙነት አላችሁ እየተባሉ የሚታሰሩ ሰዎችንም ይመለከታል። ከረጅም ጊዜ ጀምሮ የሚከነክነኝ ነገር ነው። ምክንያቱ ደግሞ ኢቲቪ የሚያቀርባቸው ዶክመንታሪዎች ናቸው፤ በሽብርተኝነት ወይም በሌላ በከባድ ወንጀል ዜጎች ተጠርጥረዋል በተባሉ ማግስት በኢቲቪ ስለጥፋታቸው ፕሮግራም ሲሰራ ባየሁ ቁጥር እነዚህ ሰዎች ስቃይ ካልተፈጸመባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እንኳን ሳይታይ ራሳቸውን እየወቀሱ እና ጥፋተኝነታቸውን እያመኑ በኢቲቪ ይቀርባሉ እያልኩ እጠይቃለሁ። ይህን እንድል የሚያደርገኝ ሌላ ማንም አይደለም፤ ያ የፈረደበት ህገ መንግስት ነው። ስለ ህገ መንግስታዊ ስር አቱ እና ስለ ህግ የበላይነት የሚጨነቁ ወይም እንጨነቃለን የሚሉ ህገ መንግስት የሚባለው ስለመብቶች የሚዘረዝረው ክፍሉንም የሚጨምር መሆኑን የህግ የበላይነትም ተጠርጣሪን በማሰር ብቻ ሳይሆን መብቱንም በማክበር የሚገለጽ መሆኑን ደጋግመን ልናስታውሳቸው ይገባል። ለመሆኑ ከላይ ከ ኢቲቪ ዶክመንታሪዎች ጋር አያይዤ ያነሳሁት ት ዝብት ምን ህገ መንግስታዊ መሰረት አለው? ተከተሉኝ።

የህገ መንግስቱ አንቀጽ አስራ ዘጠኝ በወንጀል ተጠርጥረው የተያዙ ሰዎች ስላላቸው መብት ይዘረዝራል፤ ብዙ ሰው የሚያውቀውና ደጋግሞ የሚናገረው መብት የተያዙ ሰዎች በ አርባ ስምንት ሰ አታት ውስጥ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት አላቸው የሚለው ነው። ዞን ናይኖችንና አብረዋቸው የታሰሩትንም በተመለከተ በእሁድ ፍርድ ቤት ተከፍቶ ይሄ መብታቸው ተከብሯል ተብለናል።

ጥያቄው በዚሁ አንቀጽ የተዘረዘሩ ሌሎች መብቶችስ ተከብረውላቸዋል ወይ የሚለው ነው። ለምሳሌ የዚሁ አንቀጽ ን ኡስ አንቀጽ አንድ ወንጀል ፈጽመዋል በመባል “የተያዙ ሰዎች የቀረበባቸው ክስና ምክንያቶቹ በዝርዝር ወዲያውኑ በሚገባቸው ቋንቋ እንዲነገራቸው መብት አላቸው” ይለናል። ይሄ እንደተደረገ የምናውቀው ነገር የለንም። ስለ ህግ የበላይነት የሚጨነቁት የጊዜው መንግስት ሰዎች ይህን ሊያረጋግጡልን ይገባል።
ንኡስ አንቀጽ ሁለት ደግሞ “የተያዙ ሰዎች ላለመናገር መብት አላቸው፤ የሚሰጡት ቃል ፍርድ ቤት በማስረጃነት ሊቀርብባቸው እንደሚችል መረዳት በሚችሉት ቋንቋ እንደተያዙ ወዲያውኑ ማስገንዘቢያ ሊሰጣቸው መብት አላቸው” ይለናል። ይሄ በ አሜሪካ ፊልሞች ላይ ፖሊሶች ተጠርጣሪዎችን ሲይዙ ሲናገሩ በምናይበት መንገድ የኢትዮጵያም ፖሊስ ዝም ብሎ አፈፍ አድርጎ እያዳፋ መውሰድ ሳይሆን ለተጠርጣሪው “በዚህ ወንጀል ተጠርጥረህ ነው የተያዝከው፣ ዝም የማለት መብት አለህ፤ ለፖሊስ የምትሰጠው ቃል በፍርድ ቤት በማስረጃነት ሊቀርብብህ ይችላል” በማለት እንዲገልጽለት ህገ መንግስታዊ ግዴታ አለበት ማለት ነው። ታዲያ ይህ ህገ መንግስታዊ መብት ባለበት አገር እንዴት ነው ተከሳሾቹ ለኢቲቪ ዶክመንታሪ በሚጠቅም መንገድ ቃል ሲሰጡ የምናየው። መብታቸውን ስለማያውቁ ነው እንዳንል በህገ መንግስቱ መሰረት እንዲነገራቸው ይጠበቃል። ፖሊሶቹ ህገ መንግስቱን ላያውቁት ይችላሉ እንዳንል፣ ከጸደቀ ሃያ አመት ሊሆነው ነው።  እውነታውን በምርመራ ሂደት የሚያልፉት፣ መርማሪዎቹ እና የሚያዙአቸው ያውቁታል።

የህገ መንግስቱ አንቀጽ አስራ ዘጠኝ ንኡስ አንቀጽ አምስት ፖሊስ በማስገደድ ማስረጃ እንዳይቀበል ለማድረግ በ አንድ በኩል “የተያዙ ሰዎች በራሳቸው ላይ በማስረጃነት ሊቀርብ የሚችል የእምነት ቃል እንዲሰጡ ወይም ማናቸውንም ማስረጃ እንዲያምኑ አይገደዱም” ይለናል። በሌላ በኩል ደግሞ “በማስገደድ የተገኘ ማስረጃ ተቀባይነት አይኖረውም” በማለት ለማስፈረድ በሚል ሃሳብ የሚደረግን ማስገደድ ለማስቀረት ይጥራል። በዚህ ላይ የወንጀል ህጉ አንቀጽ 424 እንደዚህ ያለውን ተግባር የሚፈጽሙ ሰዎች ከወንጀል ክስ እንደማያመልጡ ይነግረናል። በዚህ ላይ ቶርቸር በ አመታት ብዛት በይርጋ የማይተለፍ ወንጀል መሆኑን ስናስብ በህግ ደረጃ ያለው ጥበቃ ቀላል ነው የሚባል አለመሆኑን እንረዳለን።

ያም ሆኖ ግን ይህን ህግ ለመተግበር የፖለቲካ ቁርጠኝነቱ ከሌለ፣ ተቋማዊ እና የ አሰራር ስነ ስ ር አቱ ካልተዘረጋ፣ ተጨማሪ የመከላከያ ሙከራዎች ካልተደረጉ ተከሳሾች ፍርድ ቤት እየቀረቡ አቤት ባሉ ቁጥር ችላ ከተባሉ ህግ ጉልበተኞች ደካሞችን የሚያደቁበት መሳሪያ እንደሆነ ይቀጥላል። ወደ ተነሳንበት ጉዳይ ስንመለስ፣ ዞን ናይኖች ከታሰሩ በኋላ በአርባ ስምንት ሰዓት ፍርድ ቤት እንደቀረቡ ቢነገረንም፣ የማንገላታት እና የማሰቃየት ተግባር እንዳይፈጸምባቸው ሊያደርጉ የሚችሉ መብቶቻቸውን ግን ተነፍገው ነው የሰነበቱት። ቶርቸር እንዳይፈጸም መከላከል ከሚቻልባቸው መንገዶች አንዱ የሆነውን ተጠርጣሪዎቹ ጠበቃ እንዲያገኙ የማድረግ መብት ከነፍግናቸው፣ ፖሊስ እነዚህ ልጆች ላይ ቤቱን ዘግቶ ምን እንደሚያደርግ እንዴት እርግጠኛ መሆን እንችላለን? ያም ይቅር፣ ቢያንስ ፍርድ ቤት ቀርበው እንደዚህ አይነት ቃል ሲናገሩ፣ ፍርድቤት ነገሩን የሚያጣራበት ወይም እንዲጣራ የሚያዝበት የተደራጀ ስርዓት ከሌለ፣ ቢያንስ ተጠርጣሪዎቹን ሃኪም አይቷቸው ተደርጓል የተባለው ነገር መፈጸሙን እንዲያረጋግጥ ካልተደረገ፣ ቶርቸር ህገ መንግስቱ ይከለክላል የሚል መፈክር ለመናገርማ የተለየ ስልጠናም ሆነ ስልጣን አይጠይቅም። ይህን ለማድረግ ግን ከፍተኛ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ይጠይቃል። አለበለዚያ ዳኛውም ቢሆን ለእኔስ ማን አለኝ ብሎ ሊፈራ ይችላል። የአሰራር ስርዓቱ አስቀድሞ ካልተዘጋጀ አንድ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ዳኛ ለእንደዚህ አይነት ነገር ምን አይነት ምላሽ መስጠት እንዳለበት ስለማያውቅ ያለው አማራጭ “ቶርቸር እኮ በህገ መንግስቱ ተከልክሏል” ማለት ብቻ ይሆናል።
ታሳሪዎቹ ለ አስር ቀን ሙሉ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው ጠበቃ እንዳያገኛቸው ስለተደረገበት ምክንያት ጠበቃቸው ሲገልጽ፣ ፖሊስ ሌላ ስራ ይበዛብኛል እያለ ነው ብሎናል። የህግ ባለሙያ እኮ እንዲያገኛቸው የሚያስፈልገው ፖሊስ እንዳያሰቃያቸው፣ እነሱን ከ አለም ሁሉ ነጥሎ እያስፈራራም እያታለለም ራሳቸውን የሚወነጅሉበት ቃል እንዲሰጡ እንዳያደርግ ነው። ነገ ጠበቃ እንኳን ሳያገኛቸው የሰጡትን ቃል ኢቲቪ ላይ ፕሮፓጋንዳ ሲሰራበት ስናይ የህግ የበላይነት አድናቂዎች ምንም የመብት ጥሰት እንዳልተፈጠረ በፕሮግራሙ ላይ እንድንወያይ ይጠይቁን ይሆናል። እድሜ ይስጠን ብቻ።

ቸር ይግጠመን!!

ቶርቸር ይርጋ የሌለው ወንጀል ነው(ክፍል ሁለት)

ቀደም ባለው ጽሁፍ ስለ ጭቃኔ ስለተሞላበት ማሰቃየት የተወሰኑ ሃሳቦችን ወርውሪያለሁ። በወንጀል ተጠርጥረዋል ተብለው በእስር ቤት ከሚገኙት የዞን ናይን አባላት መካከል ፍርድ ቤት ቀርበው ፖሊስ የውስጥ እግራቸውን በመደብደብ የማሰቃየት ተግባር እንደፈጸመባቸው ተናግረዋል የሚለውን አሰቃቂ ዜና ከሰማሁ በኋላ ነበር አስተያየቱን የሰጠሁት። የልጆቹን ያንን ማለት ተከትሎ ፖሊስ ድርጊቱን አልፈጸምንም በሚል ስሜት ማስረጃ የላቸውም አለ መባሉንና ቶርቸር ህገ መንግስታዊ አለመሆኑን መግለጹንም ሰምተናል። የኢትዮጵያ ፖሊስ እንዲህ አያደርግም አይባል ነገር በታሪካችን እና በተሞክሮአችን አስቀያሚ ነገሮችን ያለፍን ህዝቦች ነን። እንደዚህ አይነት ነገር በራሳችንና በምንወዳቸው ሰዎች ላይ ሲፈጸም እንደማንፈልገው ሁሉ በሌሎችም ሰዎች ላይ እንዳይፈጸም ከልባችን የምንፈልግ ከሆነ እንደዚህ አይነት አቤቱታዎችን ቶርቸር ህገ መንግስታዊ አይደለም ከሚል የ አፍ ቸርነት ባለፈ እርምጃዎች መውሰድ አለብን።
እርምጃ መውሰድ ሲባል ምን ማለት ነው የሚለው ላይ ነው በዚህ ጽሁፍ የተወሰነ ነገር ለማለት የምሞክረው። በመጀመሪያ ቶርቸር እጅግ ሰልጥነናል እያሉ በሚመጻደቁ ህዝቦች እየተፈጸመ አንዳንዴ ሲጋለጥ እጅግ አሳፋሪ ቅሌት እየሆነ ያስቸገረ በተለይም ከመስከረም አስራ አንድ ጥቃት በኋላ እና ከኢራቅ አቡግራይብ እስር ቤት የ አሜሪካና የ አጋሮቿ ሃይል የፈጸመውን የሰ ብ አዊ መብት ጥሰት አምንስቲ ኢንተርናሽናል ካጋለጠ በኋላ በእጅጉ አነጋጋሪ የሆነ ጉዳይ ነው። አሁን እኛ የምናወራው ሳሙኤል ጃክሰን በተወነበት Unthinkable በተሰኘ ልብወለድ ፊልም እንደታየው ሶስት ትላልቅ ከተሞችን የሚያወድም ቦንብ ቀብሮ ቃል አልተነፍስም ስለሚል አይነት አሸባሪ አይደለም። እንደዛ ባለው ሁኔታ ስለምንወስደው አቋም በመከራከር ላይሆን የሚችለውን ወይም ከስንት አንዴ የሚሆነውን ሁሌ እንደሚሆን በማስመሰል ትኩረታችንን ከሚሻው ጉዳይ ቀልባችንን ማራቅ አይገባም። ከዚያ ይልቅ ከጎናችን እየተወሰዱ “በህግ ጥላ ስር” ከሆኑ በኋላ እንዲህ አይነት ነገር ተፈጸመብን ሲሉ ምን አይነት ምላሽ ሊኖር ይገባል? እንዲህ አይነት ነገር እንዳይከሰትስ ምን አይነት ጥንቃቄ መወሰድ አለበት? ስለሚለው ነው መጨነቅ ያለብን።
መጀመሪያ የዞን ናይኖችን ጉዳይ እንደ መነሻ እናድርገው እንጅ ይሄ ጉዳይ ከሙስሊም መፍት ሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት መታሰር እና በሽብርተኝነት ከተፈረጁ አካላት ጋር ግንኙነት አላችሁ እየተባሉ የሚታሰሩ ሰዎችንም ይመለከታል። ከረጅም ጊዜ ጀምሮ የሚከነክነኝ ነገር ነው። ምክንያቱ ደግሞ ኢቲቪ የሚያቀርባቸው ዶክመንታሪዎች ናቸው፤ በሽብርተኝነት ወይም በሌላ በከባድ ወንጀል ዜጎች ተጠርጥረዋል በተባሉ ማግስት በኢቲቪ ስለጥፋታቸው ፕሮግራም ሲሰራ ባየሁ ቁጥር እነዚህ ሰዎች ስቃይ ካልተፈጸመባቸው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እንኳን ሳይታይ ራሳቸውን እየወቀሱ እና ጥፋተኝነታቸውን እያመኑ በኢቲቪ ይቀርባሉ እያልኩ እጠይቃለሁ። ይህን እንድል የሚያደርገኝ ሌላ ማንም አይደለም፤ ያ የፈረደበት ህገ መንግስት ነው። ስለ ህገ መንግስታዊ ስር አቱ እና ስለ ህግ የበላይነት የሚጨነቁ ወይም እንጨነቃለን የሚሉ ህገ መንግስት የሚባለው ስለመብቶች የሚዘረዝረው ክፍሉንም የሚጨምር መሆኑን የህግ የበላይነትም ተጠርጣሪን በማሰር ብቻ ሳይሆን መብቱንም በማክበር የሚገለጽ መሆኑን ደጋግመን ልናስታውሳቸው ይገባል። ለመሆኑ ከላይ ከ ኢቲቪ ዶክመንታሪዎች ጋር አያይዤ ያነሳሁት ት ዝብት ምን ህገ መንግስታዊ መሰረት አለው? ተከተሉኝ።
የህገ መንግስቱ አንቀጽ አስራ ዘጠኝ በወንጀል ተጠርጥረው የተያዙ ሰዎች ስላላቸው መብት ይዘረዝራል፤ ብዙ ሰው የሚያውቀውና ደጋግሞ የሚናገረው መብት የተያዙ ሰዎች በ አርባ ስምንት ሰ አታት ውስጥ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት አላቸው የሚለው ነው። ዞን ናይኖችንና አብረዋቸው የታሰሩትንም በተመለከተ በእሁድ ፍርድ ቤት ተከፍቶ ይሄ መብታቸው ተከብሯል ተብለናል።
ጥያቄው በዚሁ አንቀጽ የተዘረዘሩ ሌሎች መብቶችስ ተከብረውላቸዋል ወይ የሚለው ነው። ለምሳሌ የዚሁ አንቀጽ ን ኡስ አንቀጽ አንድ ወንጀል ፈጽመዋል በመባል “የተያዙ ሰዎች የቀረበባቸው ክስና ምክንያቶቹ በዝርዝር ወዲያውኑ በሚገባቸው ቋንቋ እንዲነገራቸው መብት አላቸው” ይለናል። ይሄ እንደተደረገ የምናውቀው ነገር የለንም። ስለ ህግ የበላይነት የሚጨነቁት የጊዜው መንግስት ሰዎች ይህን ሊያረጋግጡልን ይገባል።
ንኡስ አንቀጽ ሁለት ደግሞ “የተያዙ ሰዎች ላለመናገር መብት አላቸው፤ የሚሰጡት ቃል ፍርድ ቤት በማስረጃነት ሊቀርብባቸው እንደሚችል መረዳት በሚችሉት ቋንቋ እንደተያዙ ወዲያውኑ ማስገንዘቢያ ሊሰጣቸው መብት አላቸው” ይለናል። ይሄ በ አሜሪካ ፊልሞች ላይ ፖሊሶች ተጠርጣሪዎችን ሲይዙ ሲናገሩ በምናይበት መንገድ የኢትዮጵያም ፖሊስ ዝም ብሎ አፈፍ አድርጎ እያዳፋ መውሰድ ሳይሆን ለተጠርጣሪው “በዚህ ወንጀል ተጠርጥረህ ነው የተያዝከው፣ ዝም የማለት መብት አለህ፤ ለፖሊስ የምትሰጠው ቃል በፍርድ ቤት በማስረጃነት ሊቀርብብህ ይችላል” በማለት እንዲገልጽለት ህገ መንግስታዊ ግዴታ አለበት ማለት ነው። ታዲያ ይህ ህገ መንግስታዊ መብት ባለበት አገር እንዴት ነው ተከሳሾቹ ለኢቲቪ ዶክመንታሪ በሚጠቅም መንገድ ቃል ሲሰጡ የምናየው። መብታቸውን ስለማያውቁ ነው እንዳንል በህገ መንግስቱ መሰረት እንዲነገራቸው ይጠበቃል። ፖሊሶቹ ህገ መንግስቱን ላያውቁት ይችላሉ እንዳንል፣ ከጸደቀ ሃያ አመት ሊሆነው ነው።  እውነታውን በምርመራ ሂደት የሚያልፉት፣ መርማሪዎቹ እና የሚያዙአቸው ያውቁታል።

የህገ መንግስቱ አንቀጽ አስራ ዘጠኝ ንኡስ አንቀጽ አምስት ፖሊስ በማስገደድ ማስረጃ እንዳይቀበል ለማድረግ በ አንድ በኩል “የተያዙ ሰዎች በራሳቸው ላይ በማስረጃነት ሊቀርብ የሚችል የእምነት ቃል እንዲሰጡ ወይም ማናቸውንም ማስረጃ እንዲያምኑ አይገደዱም” ይለናል። በሌላ በኩል ደግሞ “በማስገደድ የተገኘ ማስረጃ ተቀባይነት አይኖረውም” በማለት ለማስፈረድ በሚል ሃሳብ የሚደረግን ማስገደድ ለማስቀረት ይጥራል። በዚህ ላይ የወንጀል ህጉ አንቀጽ 424 እንደዚህ ያለውን ተግባር የሚፈጽሙ ሰዎች ከወንጀል ክስ እንደማያመልጡ ይነግረናል። በዚህ ላይ ቶርቸር በ አመታት ብዛት በይርጋ የማይተለፍ ወንጀል መሆኑን ስናስብ በህግ ደረጃ ያለው ጥበቃ ቀላል ነው የሚባል አለመሆኑን እንረዳለን።
ያም ሆኖ ግን ይህን ህግ ለመተግበር የፖለቲካ ቁርጠኝነቱ ከሌለ፣ ተቋማዊ እና የ አሰራር ስነ ስ ር አቱ ካልተዘረጋ፣ ተጨማሪ የመከላከያ ሙከራዎች ካልተደረጉ ተከሳሾች ፍርድ ቤት እየቀረቡ አቤት ባሉ ቁጥር ችላ ከተባሉ ህግ ጉልበተኞች ደካሞችን የሚያደቁበት መሳሪያ እንደሆነ ይቀጥላል። ወደ ተነሳንበት ጉዳይ ስንመለስ፣ ዞን ናይኖች ከታሰሩ በኋላ በአርባ ስምንት ሰዓት ፍርድ ቤት እንደቀረቡ ቢነገረንም፣ የማንገላታት እና የማሰቃየት ተግባር እንዳይፈጸምባቸው ሊያደርጉ የሚችሉ መብቶቻቸውን ግን ተነፍገው ነው የሰነበቱት። ቶርቸር እንዳይፈጸም መከላከል ከሚቻልባቸው መንገዶች አንዱ የሆነውን ተጠርጣሪዎቹ ጠበቃ እንዲያገኙ የማድረግ መብት ከነፍግናቸው፣ ፖሊስ እነዚህ ልጆች ላይ ቤቱን ዘግቶ ምን እንደሚያደርግ እንዴት እርግጠኛ መሆን እንችላለን? ያም ይቅር፣ ቢያንስ ፍርድ ቤት ቀርበው እንደዚህ አይነት ቃል ሲናገሩ፣ ፍርድቤት ነገሩን የሚያጣራበት ወይም እንዲጣራ የሚያዝበት የተደራጀ ስርዓት ከሌለ፣ ቢያንስ ተጠርጣሪዎቹን ሃኪም አይቷቸው ተደርጓል የተባለው ነገር መፈጸሙን እንዲያረጋግጥ ካልተደረገ፣ ቶርቸር ህገ መንግስቱ ይከለክላል የሚል መፈክር ለመናገርማ የተለየ ስልጠናም ሆነ ስልጣን አይጠይቅም። ይህን ለማድረግ ግን ከፍተኛ የፖለቲካ ቁርጠኝነት ይጠይቃል። አለበለዚያ ዳኛውም ቢሆን ለእኔስ ማን አለኝ ብሎ ሊፈራ ይችላል። የአሰራር ስርዓቱ አስቀድሞ ካልተዘጋጀ አንድ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ዳኛ ለእንደዚህ አይነት ነገር ምን አይነት ምላሽ መስጠት እንዳለበት ስለማያውቅ ያለው አማራጭ “ቶርቸር እኮ በህገ መንግስቱ ተከልክሏል” ማለት ብቻ ይሆናል።
ታሳሪዎቹ ለ አስር ቀን ሙሉ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ው ለው ምርመራ እየተደረገባቸው ጠበቃ እንዳያገኛቸው ስለተደረገበት ምክንያት ጠበቃቸው ሲገልጽ፣ ፖሊስ ሌላ ስራ ይበዛብኛል እያለ ነው ብሎናል። የህግ ባለሙያ እኮ እንዲያገኛቸው የሚያስፈልገው ፖሊስ እንዳያሰቃያቸው፣ እነሱን ከ አለም ሁሉ ነጥሎ እያስፈራራም እያታለለም ራሳቸውን የሚወነጅሉበት ቃል እንዲሰጡ እንዳያደርግ ነው። ነገ ጠበቃ እንኳን ሳያገኛቸው የሰጡትን ቃል ኢቲቪ ላይ ፕሮፓጋንዳ ሲሰራበት ስናይ የህግ የበላይነት አድናቂዎች ምንም የመብት ጥሰት እንዳልተፈጠረ በፕሮግራሙ ላይ እንድንወያይ ይጠይቁን ይሆናል። እድሜ ይስጠን ብቻ።

ቸር ይግጠመን!!

ቶርቸር ይርጋ የሌለው ወንጀል ነው(ክፍል ሁለት)


ቶርቸር/torture/ ይርጋ የሌለው ወንጀል ነው(ክፍል አንድ)

በቅርቡ ፍርድ ቤት የቀረቡት የዞን ናይን አባላት ፖሊስ የማሰቃየት ተግባር ፈጽሞብናል ብለው ለፍርድ ቤቱ ሲናገሩ ፖሊስ ማስረጃ የላቸውም በማለት ማስተባበሉንና ፍርድ ቤቱም ቶርቸር ህገ መንግስታዊ አይደለም የሚል አስተያየት መስጠቱን ሰምተናል። ዞን ናይኖቹ አቤቱታውን ያቀረቡት ፍርድ ቤቱ መፍት ሄ እንዲሰጣቸው እንጅ በህገ መንግስቱ መከልከሉን ለፖሊስ እንዲያስረዳላቸው እንዳልሆነ ግልጽ ነው። በ አንደበትማ ከሰለጠንን በጣም ቆየን እኮ። ገና በንጉሱ ዘመን ነው ከ አገር ቀድመን የ አለም አቀፍ የሰ ብ አዊ መብት ድንጋጌ(Universal Declaration on Human Rights) ሲረቀቅና ሲጸድቅ እኛም ነበርንበት። ንጉሱ ህገ መንግስታቸውን ሲከልሱም ከዚሁ ድንጋጌ የወሰዷቸውን አንዳንድ መብቶች ለተገዥዎቻቸው ሰጥተው ነበር። በዚሁ የስልጣኔ መንፈስም ነበር የድሮው የወንጀል ህግ ሲረቀቅ ዘርማጥፋትን የመሳሰሉ የ አለም አቀፍ ወንጀሎች የህጋችን አካል የነበሩት። የሚገርመው ግን ንጉሱን ጥሎ የመጣው ደርግ በቀይ ሽብር ያንን ሁሉ ግፍና ወንጀል ሲፈጽም “ኧረ እንዴት ነው ንጉሱ ያጸደቁት የወንጀል ህግ እንዲህ የሚል አንቀጽ አለው” ያለ አልነበረም። ከነበረም የሰማው የለም። 

አሁንም ዘመናዊ ለመምሰል ህግ ከማውጣት እና ከማጽደቅ፣ ህጉን ሁሉ ችላ ብሎ የፖለቲካ ፉክክሩ ላይ ትኩረት ከማድረግ አልወጣንም። የጊዜው መንግስት ሰዎች ራሳቸውን ከደርግ ጋር እያነጻጸሩ የተሻሉ በመሆናቸው ምስጋና ከመጠበቅ፣ በ አገሪቱ ውስጥ ያሉትን ህጎች ከማክበር አንጻር ያሉበትን ደረጃ እያስተዋሉ እንቅልፍ ቢያጡ ነው የሚሻለው፤ አለበለዚያ በደርግ ሰዎች ላይ የደረሰው በእነሱም ላይ መድረሱ አይቀርም። ምክንያቱም ግልጽ ነው።
የጊዜው ህገ መንግስት ጭካኔ የተሞላበት የማሰቃየት ተግባርን ቀርቶ፣ ኢሰብ አዊ የሆነ ማንኛውንም አያያዝ የሚከለክል ነው። ከዚያም አልፎ ኢትዮጵያ ያጸደቀቻቸው አለም አቀፍ ድንጋጌዎች ሁሉ የህገ መንግስቱ አካል ናቸው የሚል ነው። ያም አልበቃ ብሎ የህገ መንግስቱ ሰ ብ አዊ መብት ነክ አንቀጾች ኢትዮጵያ ባጸደቀቻቸው የሰብ አዊ መብት ስምምነቶች መሰረት መተርጎም እንዳለባቸው ያዛል። ይህን ሁሉ እውነት የኢትዮጵያ ህገ መንግስት አንድ ሶስተኛው የሰ ብ አዊ መብት ድንጋጌ ነው ብሎ በከንቱ ለመመጻደቅ ብቻ መጠቀም አይቻልም። ኢትዮጵያ የማሰቃየት ተግባር የሚከለክለው የተባበሩት መንግስታት ጸረ ቶርቸር ስምምነት የፈረመችና ያሰደቀች አገር ናት። ያ ማለት የዚሁ ስምምነት አንቀጾች የ አገሪቱ የህግ አካል ናቸው ማለት ነው።

አለም አቀፍ ህጉን ብንተወው እንኳን አሁን ባለው የኢትዮጵያ የወንጀል ህግ መሰረት አሰቃይቶ ቃል መቀበል ድርጊቱን የፈጸመውንም ሰው እስከ አስር አመት ድርጊቱን ያዘዘውን ባለስልጣን እስከ አስራ አምስት አመት ሊያሰቀጣ የሚችል ወንጀል ነው። ከጥቂት ቀናት በፊት ለተባበሩት መንግስታት የሰ ብ አዊ መብቶች ጉባ ኤ የኢትዮጵያን የሰ ብ አዊ መብት አያያዝ ሲገመግም የኢትዮጵያ ተወካዮች የ አገሪቱ ስ ር አት ቶርቸርን እንደማይታገስ ገልጸው ነበር። በህግማ በንጉሱ ጊዜ ጀምሮ ሰልጥነናል፤ ልባችን አልሰለጠነም እንጅ። ይህንን ድርጊት የመከላከል ተግባር ከፍተኛ የፖለቲካ ቁርጠኝነት የሚጠይቅ፣ ተገቢ ተቋማዊና ህጋዊ ማእቀፍ፣ የነቃ ክትትልና የእርማት ስር አት የሚፈልግ ነገር ነው።

ይሄ ሁሉ በ አብዛኛው ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሌለ ለማወቅ የኢትዮጵያን እስር ቤቶች ዞሮ መጎብኘት አያስፈልግም። ይሄው በዞን ናይን አባላት፣ በፖሊስ እና በፍርድ ቤት መካከል ተደረገ የተባለው ምልልስ በራሱ ብዙ የሚያስጨብጠን ቁምነገር አለ። አንዳንድ አጠቃላይ ነጥቦችን ላስቀምጥ።

፩ኛ በደርግ ጊዜ ይፈጸም ስለነበረው ኢ ሰብ አዊ የማሰቃየት ተግባር ጉዳቱ የደረሰባቸው ሰዎች ከሚናገሩት፣ በቀይ ሽብር የፍርድ ሂደት ከተገለጡ እውነቶች ብዙ ነገር ተምረናል። ጥቅም ላይ ይውሉ ስለነበሩት የማሰቃያ ቴክኒኮች አዲስ አበባ የሚገኘውን የቀይ ሽብር ሰማእታት ሃውልት መታሰቢያ ጎራ ብሎ በመጎብኘት መረዳት ይቻላል። በዚሁ መታሰቢያ በር ላይ “በፍጹም አይደገምም” የሚል ጽሁፍ ተጽፏል። አሁን ዋናው ጥያቄ በእርግጥ ከዚህ አሰቃቂ ታሪክ ተሻግረን ሄደናል ወይ የሚለው ነው። “አዎ ተሻግረናል፤ አዎ ኢሰብ አዊ የማሰቃየት ተግባር በእስረኞች ላይ አይፈጸምም”፣ ብሎ በእውነትና በድፍረት የሚነግረን ሰው ቢኖር ደስ ባለኝ። እንዳይኖር ስለምንመኝ ብቻ የለም እያልን በእኛም ዘመን እንደዛ ካለው አሰቃቂ ታሪክ መፈጸም ማምለጥ አንችልም።
፪ኛ የሚያስፈልገው መፈክር መደጋገም ሳይሆን እንደዚህ አይነት ተግባር እንዳይፈጸም የሚያስችል የህግ፣ የተቋማትና የ አሰራር ስር አት መዘርጋት ነው። ያ እስካልተፈጸመ ድረስ ማንም በመንግስት ሃላፊነት ላይ ያለ ሰው ራሱ በቀጥታ ስላላደረገው ብቻ ከእንደዚህ አይነቱ ነውረኛ ወንጀል ተጠያቂነት አያመልጥም። ሰ ብ አዊ መብት የሚባል ጽንሰ ሃሳብ በማይታወቅበት ዘመን ሚኒሊክ እንዲህ ወይም እንዲያ ያለውን ወንጀል ፈጽሟል እያልን ስንመጻደቅ የምንውል ሰዎች ራሳችን እያጨበጨብን ያጸደቅነውን ህገ መንግስትና ሌሎች ህጎች በ አሳፋሪ መንገድ ችላ ብንለው ከታሪክ እና ከፖለቲካ ተጠያቂነት ባሻገር ከህግ ተጠያቂነትም አናመልጥም።

የሚገርመው ነገር የኢትዮጵያ ህገ መንግስት ራሱ በአንቀጽ ሃያ ስምንት ላይ በስብዕና ላይ ስለሚፈጸሙ ወንጀሎች ሲደነግግ ከሌሎች አለም አቀፍ ወንጀሎች ባሻገር፣ ቶርቸር ወይም ኢ ሰብዐዊ የድብደባ ድርጊቶችን በፈጸሙ ሰዎች ላይ ክስ ማቅረብ በይርጋ አይታገድም ይለናል። ያ ማለት የዛሬ አምሳ እና ስድሳ አመት ራሱ ዛሬ በየትኛውም የኢትዮጵያ እስርቤት ሰዎችን በ አሰቃቂ ሁኔታ የሚያሰቃዩ ሰዎች ከቤተሰቦቻቸው እየተነጠቁ ወደ እስር ቤት ይላካሉ። ደርግ የ ሃይለ ስላሴን የወንጀል ህግ ችላ ብሎ በሰራው ወንጀል ከቅጣት እንዳላመለጠ፣ የጊዜው መንግስት ሰዎችም “ለህገ መንግስታዊ ስ ር አቱ መከበር በሚል” ሰበብ ለሚሰሩት ጸያፍ ተግባር ከተጠያቂነት አያመልጡም።

Tuesday 22 April 2014

የማንነት ብዙነትና ወሳኝ ማንነት

ኤርትራን ነጻ አገር መሆን ተከትሎ በጥቂት አመታት ውስጥ የኢትዮጵያና ኤርትራ ጦርነት ሲጀመር በብዙ አስር ሽዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ወደ ኤርትራ ተባረሩ፤ ከተባረሩት ውስጥ ቀላል የማይባል ቁጥር ያላቸው ተፈናቃዮች ተወልደው ካደጉባቸው የኢትዮጵያ አካባቢዎች ጋር ያላቸው ምስ ስል እና ቅርበት በዘር ሀረግ ከሚዛመዱት ኤርትራ ማህበረሰብ ጋር ካላቸው ምስ ስል የበለጠ እንደነበር ግልጽ ነው። ኢትዮጵያ ለመፈናቀላቸው ኤርትራዊ ማንነታቸው ምክንያት ይሁን እንጅ፣ በሄዱበት ኤርትራ ደግሞ ብዙ ርቀት አቋርጠው ከመሄዳቸው ጋር በሚያያዝ መልኩአምቼ” መባላቸው የማንነታቸው አንዱ መገለጫ ሊሆን ችሏል፤ በኢትዮጵያ ውስጥ ሲኖሩ ኤርትራዊነታቸው የጎላውን ያህል፣ ኤርትራ ውስጥ ሲኖሩ ኢትዮጵያ መሄዳቸው ወሳኙ የማንነታቸው መገለጫ ሆኗል።

በተመሳሳይ መልኩ ዜግነት ስለሌላቸው ብቻ ተወልደው ካደጉበት አገር በተለያዩ ምክንያቶች ወደ ወላጆቻቸው አገር እንዲሄዱ የሚጠየቁ ሰዎች ተመሳሳይ ችግሮች ያጋጥሟቸዋል። ባደጉበት አገር ከሌላ አገር ከመጡ ወላጆች መወለዳቸው ጎልቶ የሚታይ በመሆኑ ወሳኝ ማንነታቸው እሱ እንደሆነ ተደርጎ ቢቀርብም እውነተኛ አገራቸው ወደተባለው አገር ሲሄዱ ግን ካደጉበት አገር የወረሱት ቋንቋ፣ ባህል   አመለካከት እና ሌሎችም ዝንባሌዎች ጎልተው ይወጣሉ። ከልጅነታቸው ጀምሮ አሜሪካ አድገው በወንጀልና በህገወጥነት ምክንያቶች ወደ ሌሎች አገራት እየተባረሩ ያሉ ሰዎችን በዜግነት አሜሪካዊ ባይሆንም አገሪቱ ጋር ባላቸው ቁርኝት የተነሳ ተባረው በሚሄዱበት ቦታ እንደ አሜሪካ ስደተኞች እንደሚኖሩ ለማሳየት Daniel Kantstroom የተባለ ስድተኞችን በተመለከቱ ህጎች ዙሪያ የታወቀ ምሁር እነዚህን ሰዎች  “the new American Diaspora” በማለት ይገልጿቸዋል። 
ከዚህ ጋር አያይዘን በተለያዩ ጊዚያት ወደ እስራ ኤል የተጓዙ ቤተ እስራኤላውያንንም ማንሳት ይቻላል። ኢትዮጵያ ውስጥ እያሉ ጎልቶ የሚታየው የማንነታቸው መልክ እስራ ኤል ጋር ያላቸው ቁርኝት ቢሆንም እስራ ኤል ውስጥ ደግሞ ከቆዳቸው ቀለም ጀምሮ ኢትዮጵያዊ መነሻቸው የማንነታቸው ጉልህ መገለጫ የሚሆንበት ብዙ አጋጣሚ አለ።

ከላይ የተጠቀሱት ምሳሌዎች ማንነት አንድና ወጥ እንዳልሆነ ከማሳየት አልፈው በተለያዩ ሁኔታዎች ጎልቶ የሚወጣው የ አንድ ሰው የማንነት ገጽታ የተለያየ ሊሆን እንደሚችል የሚያመላክቱ ይመስለኛል። ማንነት፣ ምስ ስልና ልዩነትን፣ ርቀትና ቅርበትን፣ እንዲሁም መዛመድንና አለመዛመድን መሰረት አድርጎ የሚደረግ ክፍፍልንና መቧደንን የምንረዳበት፣ የምንገልጽበትና የምንተነትንበት ጽንሰ ሃሳብ ነው። የምንመሳሰልባቸው እና የምንለያይባቸው፣ የምንራራቅባቸውና የምንቀራረብባቸው፣ የምንዛመድባቸውና የማንዛመድባቸው ነገሮች በጣም ብዙ ስለሆኑ የተለያዩ ማንነቶች ይፈጥሩልናል። የወላጅ፣ አያት፣ ቅድመ አያት ወዘተ መጋራት ቤተሰብነትና ዝምድናን ይፈጥራል፤ በጾታ መመሳሰል የጾታ ማንነትን ይፈጥራል፤ በሃይማኖት መመሳሰል የሃይማኖት ማንነትን ይፈጥራል፤ በቋንቋ መመሳሰል፣ የቋንቋ ማንነትን ይፈጥራል፤ አገር መሳሰል፣ አገር ማንነትን ይፈጥራል፣ አህጉር መመሳሰል አህጉራዊ ማንነትን ይፈጥራል፤ በፖለቲካ አቋም መመሳሰል የፖለቲካ ማንነትን ይፈጥራል፤ በቆዳ ቀለም መመሳሰል፣ የቀለም ማንነትን ይፈጥራል። አንድ ሰው ልብስ ደራርቦ እንደሚለብሰው ሁሉ እነዚህን የተለያዩ የማንነት መገለጫዎችንም ደራርቦ ይይዛል። ከነዚህ ሁሉ ማንነቶች ጀርባ ሰው በሰውነቱ ከሁሉም ሰዎች ጋር የሚጋራው ሰብአዊ ማንነት አለው።

ከዚህ በመነሳት ስለ ማንነት የተወሰኑ ምልከታዎችን ማድረግ የምንችል ይመስለኛል። አንድ ሰው ካሉት ተደራራቢ ማንነቶች ውስጥ አስበልጦ የሚያየውን ሊወስን ይችላል። ነገር ግን ይሄ ውሳኔ ከሚኖርበት ከባቢ ተጽእኖ ነጻ መሆን የሚችል አይደለም። ይሄ የሆነበት አንዱ ምክንያት የሚኖርበት ባህላዊ፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ከባቢ አጉልቶ የሚያያቸው የማንነት አይነቶች ሊኖሩ ስለሚችሉ ነው። ራሱ አስበልጦ የሚያየው የማንነቱ ቀለም እና ሌሎች ሰዎች አጉልተው የሚያዩት የማንነቱ ቀለም አንድ ላይሆን መቻሉም ሌላው ገዳቢ ነገር ነው። ለምሳሌ ባሁኑ አት አለም ህዝብ በዋነኝነት የተከፋፈለው እና የተቧደነው አገራት እንደመሆኑ አንድ ግለሰብ ከሁሉም አስበልጬ የማየው ማንነቴ ሰው መሆኔን ነው በማለት ብቻ በፈለገው አገር ሄዶ የመኖር እድል አያገኝም። ወይም ደግሞ እምነት ከማይመሳሰሉኝ ኢትዮጵያዊያን በእምነት የሚመሳሰሉኝ የሳውዲ ሰዎች ይበልጡብኛል ብሎ የሚያስብ ኢትዮጵያዊ በህገ ወጥነት ወደ አገርህ ሂድ ተብሎ ከመባረር አይድንም፤ከላይ መግቢያው አካባቢ በተጠቀሰው አይነት ሰዎች ጥርስ ነቅለው ካደጉበት አገር ወደአገራችሁ” ሂዱ እየተባሉ የሚባረሩበት እውነት ይህ አለም የሰዎች ሳይሆን አገሮች ነው እንድንል ያስገድደናል።

ከሁሉም የማስበልጠው የ ትግራይ ማንነቴን ነው፣ በዚህም ከ ትግርኛ ተናጋሪ ኤርትራውያን ጋር ያለኝ ዝምድና ይበልጥብኛል የሚል ሰው፣ በ ኤርትራ ሲኖር በሌሎች ዘንድ ከትግራይ መምጣቱ የጎላ የማንነቱ መገለጫ ተደርጎ እንዳይታይ መከላከል ይከብደዋል። ከሁሉም የማስበልጠው አማራ መሆኔን ነው የሚል አንድ የጎጃም አካባቢ ሰው፣ ወደ ጎንደር ቢሄድ የጎጃሜነት ማንነቱን ደጋግሞ እንዲያስታውስ የሚያደርግ ከባቢ ውስጥ ሊኖር እንደሚችል መገመት ይቻላል። ከሁሉም የማስበልጠው ማንነቴ ጎጃሜ መሆኔን ነው የሚል ሰው ወደ ኦሮምያ ወይም ደቡብ ክልል ቢሄድ ጎልቶ የሚጠቀስለት ማነነቱ አማራነቱ ሊሆን እንደሚችልም መገመትም ይቻላል።

ከሌላ አገር በስደት ከመጡ ወላጆች ተወልደው የሚያድጉ ህጻናት ከሚገጥማቸው ማንነት ነክ ፈተና አንዱ ባደጉበት አገር ከሌላ አገር ጋር ያላቸው የትውልድ ቁርኝት እነሱ ባይፈልጉት እንኳን በዙሪያቸው ባሉ ሰዎች ጎልቶ የሚታይ መሆኑ ነው። እነሱ ተወልደው ካደጉበት አገርና አካባቢ ያገኙትን ማንነት ማጉላት ቢፈልጉ እንኳን በዙሪያቸው ያሉ ሰዎች ወላጆቻቸው የመጡበትን አካባቢ እና ከዚያም የሚቀዳውን ማንነት ደጋግመው ያስታውሷቸዋል። ማንነት መመሳሰልንና ልዩነትን መሰረት የሚያደርግ እንደመሆኑ በ አንድ አካባቢ ውስጥ አንድን ሰው ወይም ቡድን በ አካባቢው ካሉ ሰዎች ወይም ቡድኖች ለየት የሚያደርገው የማንነቱ ቀለም ጎልቶ ይወጣል። በነጭ ወረቀት ላይ በነጭ ቀለም ቢጻፍ እንደማይታይ ሁሉ፣ በነጭ ወረቀት ላይ ከነጭ በተለየ ቀለም ሲጻፍ ጎልቶ እንደሚወታው ሁሉ በማንነት ውይይት ውስጥ ጎልቶ የሚወጣው የሚያመሳስለው ሳይሆን የሚያለያየው ነገር ነው። እስካሁን ባለው ሀተታ ወሳኝ ሊባል የሚችለው ማንነት በምርጫ እና በሁኔታዎች ሊለያይ እንደሚችል ግልጽ የሆነ ይመስለኛል። ስለዚሁ ነጥብ አንድ ተጨማሪ አስተያየት በመስጠት ይህን ጽሁፍ ላጠቃልል።


ማንነት ተኮር ግጭቶች ስለሚነሱበት እውነት እያሰብን የለምን ሁኔታ ብናስተውል በየ አካባቢው ያሉ የተለያዩ አይነት ልዩነቶች፣ ከህዝቦች ታሪካዊ መስተጋብር ጋር ተዳምረው ስር በሰደደ እና በከረረ ፉክክር፣ በጥላቻ እና በግጭት ውስጥ ጎልተው እናስተውላለን። በቋንቋ አንድ በሆኑ እንደ ሱማልያ ባሉ አገራት የጎሳ ልዩነት ጎልቶ ሊወጣ ይችላል። በደቡብና ሰሜን ኮሪያ መካከል ያለው ልዩነት መሰረቱ ርእዮታለማዊ ነው። እስልምናን በመከተል ተመሳሳይ የሆኑ ማህበረሰቦች፣ በተለያዩ ሴክቶች መካከል ባለው ልዩነት እና ፉክክር ተጠምደው ወደ ግጭት ያመራሉ። ቀደም ባለው ጊዜ በሶሻሊዝም አስተሳሰብ የተቃኙ የኢትዮጵያ አንዳንድ ወጣቶች ከብሄር ወይም ከቋንቋ ዝምድና ይልቅ መደባዊና ርእዮተ አለማዊ ወገንተኝነት የበለጠ ትርጉም የሚሰጣቸው ነገር እንደሆነ መረዳት ይቻላል። የእያንዳንዱ አገር ወይም አካባቢ ሁኔታ ራሱን በቻለ የታሪክ፣ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና ማህበራዊና ሌሎችም ዝርዝር እውነታዎች የሚወሰን አካሄድ ያለው በመሆኑ፣ በቋንቋ ይሁን በርዕዮተ አለም፣ በጎሳ ይሁን ወይም በአካባቢ፣ በሃይማኖት ይሁን ወይም ሌላ ልዩነቶችና በ አንድ አካባቢ ባለ ግጭት ግልጽ የሆነ የምክንያትና የውጤት ግንኙነት መፍጠር ይከብዳል። ቢያንስ ግን በየሁኔታው ከሚያመሳስለው ነገር ይልቅ የሚያለያየው ነገር ጎልቶ እንደሚወጣና ወሳኝ ተደርጎ እንደሚወሰድ መመልከት ይቻላል። በተጨማሪም የሚጎላው ማንነት እያንዳንዱ ግለሰብ ወይም ቡድን ለራሱ በሚመርጠው ብቻ ሳይሆን፣ ከሌሎች ሰዎች ወይም ቡድኖች ጋር በሚያደርገው መስተጋብር ከእነሱ በሚለይበትና እንዲጎላ በሚፈልጉት እንዲሁም በሌሎች ታሪካዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሁኔታዎች ሊወሰን እንደሚችል መረዳት ይቻላል።